• የደብሩ ሰበካ መንፈሳዊ አስተዳደር ጉባኤ አባላት

  • የሕንጻ አስመራቂ ኮሚቴ አባላት (አዲስ አበባ)

  • የደብሩ አገልጋዮች በከፊል

  • የደብሩ ሰንበት ት/ቤት አባላት በከፊል

መልእክታት

የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ መልዕክት

“ዛ አንቀጽ እንተ እግዚአብሔር፡፡ ጻድቃን ይበውኡ ውስቴታ፡፡ ይህች የእግዚአብሔር ደጅ ናት፤ ወደ እርስዋም ጻድቃን ይገባሉ፡፡” መዝ 117፥20

ቤተ ክርስቲያን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደሙ የመሠረታት ሰማያዊ ተቋም ናት፡፡ በእርስዋም ጻድቃን (እውነተኞች) ይመላለሱባታል፡፡ ወደ እርስዋም የገቡ ከበደላቸው ነጽተው ጽድቅን ይለብሳሉ፡፡ ጻድቃን
ቡሩካንን በውስጧ ይዛለችና ቤተክርስቲያን በምድር የምትገኝ የእግዚአብሔር መንግሥት ምሳሌ ናት፡፡ የክርስቶስ ወንጌለ መንግስት የሚነገርባት፣ ለሰው ልጆች ኃጢአት ለማስተስረይ የሚፈተተው የክርስቶስ ሥጋና የሚቀዳው
ደም ለምእመናን የሚቀርብባት ምስጢራት የሚፈጸምባት የእግዚአብሔር ደጅ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንገባ የቅድስናን ሸማ እንለብሳለን፡፡

በሰማይና በምድር የሚገኝ ሁሉ የሚታየውና የማይታየው ግዙፉና ረቂቁ ሁሉ የእርሱ የሆኑለት እግዚአብሔር የሚከበርበት ቤተ መቅደስ በእኛ በክርስቲያኖች ዘንድ ልዩ እና ገናና ክብር ያለው ስፍራ ነው፡፡

ለአምልኮተ እግዚአብሔር የተለዩ ስፍራዎች በክርስቲያኖች ሕይወት ውስጥ ልዩ ክብር አላቸው። የቤተክርስቲያን ባለቤት ክርስቶስ ካለው ልዩ ክብር አንጻር ታላቅ ክብር ለቤተ ክርስቲያን እንሰጣታለን። በአንድነት እና ፍጹም በሆነ ክርስቲያናዊ ሕብረት እግዚአብሔርን የምናገለግልባት ለሰማዩ መንግስት ዝግጅት የምናደርግባት ይህች ልዩ ስፍራ ለአገልግሎት ምቹ በሆነ መልኩ መሰራቷ ለአማንያን ፍጹም ደስታ ነው፡፡

የይርጋ ዓለም (ጋኔ) ደብረ ታቦር ቅድስት አርሴማ ወደብረ ቁስቋም ቅድስት ማርያም አብያተ ክርስቲያናት ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ የገጠር አብያተ ክርስቲያናትን በመደገፍ እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን በመንፈሳዊ አገልግሎት ብቻ ሳይሆን በሁለንተናዊ ልማት መስክም ጭምር ከፍ ብላ እንድትታይ በማደረግ ላይ የሚገኘው መልካም ሥራ ጎልቶ የሚጠቀስ ነው፡፡

ከዚህም በተጨማሪ የደብረ ቁስቋም ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውብ በሆነ ሁኔታ ተሰርቶ ተጠናቆ ለአገልግሎት በመብቃቱ ለአድባራቱ ምእመናን እንዲሁም ለመላው ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን ታላቅ ደስታ ነው፡፡

አብያተ ክርስቲያናቱ ሕሙማነ ሥጋ፤ ፈውሰ ሥጋ የሚጎናጸፉበት፣ ያዘኑ የሚጽናኑበት፤
በመከራ ውስጥ ያሉ ፍጹም እረፍትን የሚያገኙበት በመሆኑ የካህናትና ምእመናን ደስታ የላቀ ነው፡፡

በዚህ ታላቅ ሥራ በአድባራቱ አስተዳዳሪ መልአከ ሕይወት ቀሲስ እንደሻው አብርሃ መሪነት በሕንጻ ኮሚቴነትና በተለያዩ የአገልግሎት ስፍራዎች አስተዋጽኦ ያደረጋችሁ እንዲሁም ይህንን የደስታ ቀን እንድንመለከት ትብብር ያደረጋችሁ በአብያተ
ክርስቲያናቱ እና በሀገረ ስብከታችን እንዲሁም በሀገራችንና በመላው ዓለም የምትገኙ ምእመናን ሁሉ ትጋታችሁ ውጤት አምጥቷልና እንኳን ለዚህ ቀን አደረሳችሁ እንኳን ደስ አላችሁ እላለሁ፡

የአባቶቻችን አምላክ እግዚአብሔር ሀገራችንን ጽኑ ሰላም ያድርግልን፡፡ ቤተ ርስቲያንንም ይጠብቅልን፡፡ ምእመናንን በፍቅር በአንድነት ያጽናልን፡፡ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
አባ ዮሴፍ
የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ
የሲዳማ ክልል የጌዴኦ ዞን የአማሮና ቡርጂ ወረዳዎች
አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

የሀገረ ስብከቱ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ መልዕክት

“ስሜ ለዘላለም በዚያ ይኖር ዘንድ ይህን ቤት መርጫለሁ፤ ቀድሻለሁ፤ ዓይኖቼና ልቤም ዘወትር በዚያ ይሆናሉ፡፡” 2ኛ ዜና መዋ. 7፥16

ሰውና መላእክት ስሙን ቀድሰው ክብሩን ለመውረስ ተፈጥረዋል፡፡ የሰው ልጅም ከሕገ ልቦና ጀምሮ እግዚአብሔርን ሲያመሰግን መስዋዕት ሲያቀርብ ኖሯል፡፡ በሕገ ኦሪትም በደብተራ ኦሪት የነበረው ሥርዓተ አምልኮ እስከ ቅዱስ ዳዊት ድረስ ደርሷል፡፡

ታላቁ ንጉሥ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት የእግዚአብሔር የቃል ኪዳኑ ታቦት በድንኳን ሳለ እኔ ደካማውና ጎስቋላዉ ባማረና በተዋበ በልዩ ሁኔታ በተሠራ ቤት እንዴት እኖራለሁ እያለ እጅግ በጣም አዝኖ ወደ ቤተመንግሥቴም አልገባም ወደ ዙፋኔም አልወጣም በማለት ተክዞ ይኖር ነበር፡፡ እግዚአብሔር አምላክም ቤቴን የምትሠራልኝ አንተ አይደለህም ከአብራክህ የሚወጣው ልጅህ ሰሎሞን ነው ብሎታል፡፡ የዳዊት ልጅ ጠቢቡ ሰሎሞን የእሥራኤል ልጆች ከግብጽ ምድር ከወጡ ከ480 ዓመት በኋላ በነገሠ በ4ኛው ዓመት ዚፍ በሚባለው በሁለተኛው ወር የእግዚአብሔርን ቤት በመሥራት ጀምሮ
ፈጸመውም፡፡ሰሎሞን የወደደውን የልቡን ሀሳብ ሠርቶ በፈጸመ ጊዜ እግዚአብሔር በገባኦን ተገልጦለት በፊቴ የጸለይከውን ጸሎትህንና ልመናህን ሰምቼሃለው ለዘለዓለም ስሜ በዚያ ያድር ዘንድ ይህንን የሠራኸውን ቤት ቀድሻለኹ፡፡ ዓይኖቼም ልቤም በዘመኑ ሁሉ በዚያ ይሆናል በማለት ቃልኪዳን ገብቶለታል፡፡

ይህ ታሪክ የሚያስረዳን ቤተክርስቲያን ለማነጽና ለመሥራት ልበ ቅን የሆነ ሁሉ እንደሚያስብ ወደ ተግባር ለመግባት ግን የእግዚአብሔር ፈቃድ እንደሚጠይቅ ያስገነዝባል፡፡ እግዚአብሔር በረድኤት በሚገለጥባቸው ቅዱሳን መካናት ለጸሎት የሚሰበሰቡ ምእመናን በረከትን ይቀበላሉ፡፡ የኃጢአት ሥርየትንም ያገኛሉ፡፡ በቤተክርስቲያን ስብሐተ እግዚአብሔር ይደርስባታል፡፡ ሥጋውና ደሙ ለምእመናን ይቀርብባታል፡፡ መሰረቷ ክርስቶስ ቀድሷታልና ምእመናንን ከፈጣሪያቸው የሚገናኙባቸው ምስጢራት ይፈጸምባታል፡፡ ለዚህም ፍጹም መንፈሳዊ አገልግሎት ቤተክርስቲያን ምእመናን ባሉበት ስፍራ ሁሉ ትታነጻለች፡፡

በመሆኑም በሀገረ ስብከታችን ይርጋዓለምጋኔ ደ/ታ/ቅ/አርሴማወቅ/ማርያም አብያተ ክርስቲያናት አስተዳደር ስር የቅድስት ማርያም ሕንፃ ቤተክርስቲያን እግዚአብሔር አምላክ በመረጣቸው ካህናት ምዕመናንና ምዕመናት አማካይነት ተጀምሮ ተጠናቆ ለአገልግሎት ለዚህ በመብቃቱ ደስታችን ከፍ ያለ ነው፡፡

ለዚህ ህንጻ ሥራ መሳካትም ገንዘባቸውን ጉልበታቸውንና ሙሉ ጊዚያቸውን የሰጡትን፤ የአድባራቱ አስተዳዳሪና ሰበካ ጉባኤ አባላት፣ የህንፃ አሠሪ ኮሚቴ፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፣ ምዕመናንና ምዕመናትን በሙሉ እግዚአብሔር አምላክ ዋጋችሁን እንዲሰጣችሁ የዘወትር ጸሎታችን ነው፡፡ ቤተክርስቲያንን ንስሐ የምንገባባት፤ የክርስቶስ አምላካችንን ሥጋና ደም የምንቀበልባት በክብር የምናርፍባት ያድርግልን፡፡ አሜን፡፡

ወስብሐት ለአግዚአብሔር
መጋቤ ጥበባት ቀሲስ ሞላልኝ መርጊያ
የሲዳማ ክልል ሀገረ ስብከት
ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ

የወረዳዉ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ መልዕክት

“ሕንፃው ግን ለእግዚአብሔር አምላክ ነው እንጂ ለሰው አይደለምና ሥራው ታላቅ ነው።” 1 ዜና መዋ. 29፥1

“የሚመረኮዟት የሚጠጉባት ለምዕመናን ሕንጻ ዘወትር ዝግጁ የሆነች የማትነዋወጽ የሃይማኖት መሠረት ድንግል ማርያም ናት”፤ መ/አርጋኖን 3። ታላቁ መቃርስ ስለ ሕንፃ ቤተክርስቲያን በተናገረበት፤
ለንግስት እሌኒ የማይፈርስ ጥሩ ሕንፃ ልትሠሪ ይገባል፤ ከዚህ የሚተርፈውን ለድሆች እና ለችግርተኞች ስጫቸው አላት፤ ስንክሳር መስከረም 16።

የቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤና ሕንፃ አሰሪ ኮሚቴ እንደ ቅድስት እሌኒ በጸሎት በመትጋት፣ በአንድነት ሆነው ከሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ግንባታ ጎን ለጎን የገጠር አብያተ ክርስቲያናትን በማነፅ፤ ለሰራተኛ አገልጋይ ካህናት ድጎማ በመስጠት፤ አቅም ለሌላቸው አቅም በመሆን ሰርተዋል፤ እየሰሩም ይገኛሉ። የእግዚአብሔር ሕንጻ ናቸው፤ ከእርሱ ጋር አብረን የምንሰራ ነንና እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (1ኛ ቆሮ 3፥9)፤ እግዚአብሔር እብሮን ባይሰራ ኖሮ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን፣ ከ10 በላይ የሆኑ የገጠር አብያተ ክርስቲያናትን በማነፅ ካህናትን በመደጎም በአጭር ግዜ ውስጥ 2 ግዙፍ የሆኑ አብያተ ክርስቲያናትን አሳንፆ መፈጸም ባልተቻለ ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔርን በመውደዳችሁ እና በማክበራችሁ ብዙ ልማት እንድሰሩ እግዚአብሔር ረድቷችኋል፤ ቅዱስ ዳዊት አንተን ለሚወዱ ብዙ ልማት ይሁን እንዳለ፤ መዝ. 122፥6። የምትሹትንም ሁሉ አልከለከላችሁም፤ የልቡን ፈቃድ ሰጠኸው የከንፈሩንም ልመና አልከለከልኸውም እንዳለ ነቢዩ ዳዊት፤ መዝ. 21፥2።

ቅዱስ ጳውሎስ ለልጁ ለጢሞቴዎስ በእግዚአብሔር ማደሪያ ቤት መኖር እንደሚገባ ሲመክረው (ሲፅፍለት) ቤቱ የእውነት ዓምድ እና መሠረቱ የኽያው እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ነው አለ፤ 1 ጢሞ 3፥15። ይኽነን የእውነት ዓምድ ቤተ ክርስቲያን ለማሳነፅ ዳዊት ተመኝቶ አልተፈቀደለትም፤ የተፈቀደላችሁ ሰሎሞናውያን የታደላችሁ ናችሁ።

የእግዚአብሔርን ቤት ይሠሩ ዘንድ በአንድነት ቆሙ፤ እዝራ 3፥9። ሥራው የተሳካ የሆነው የደብሩ አስተዳዳሪ መ/ሕ/ ቀሲስ እንደሻው አብርሃ ከሰበካ ጉባኤው እና ከሕንፃ አሰሪው ጋር እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ እንደ አንድ ልብ መካሪ ሆነው በመስራታችው ነው። በሰላም ማሠሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ፤ ኤፌ 4፥3። በዚሁ ትጋታችን በርትተን በመሥራት ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ላልተለየን አምላክ ምስጋና ይግባውና የጀመርናቸውን የህክምና ማዕከል እና የሳሙና ፋብሪካ የግንባታ ሥራ ያስፈፅመን ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን። አሜን።

ወስብሐት ለአግዚአብሔር
መልአከ ፀሐይ ቀሲስ ሙላት ግዛው
የይርጋ ዓለም ወረዳ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ

የአብያተ ክርስቲያናቱ አስተዳዳሪ መልዕክት

‘’ፈቃዱን የምታደርጉ አገልጋዮቹ እግዚአብሔርን ባርኩ’’ መዝ. 102፥21

በቅድሚያ የተከበራችሁ ውድ የክርስቶስ ቤተሰቦች፣ የእመቤታችን የቅድስተ ቅዱሳን የድንግል ማርያም የአሥራት ልጆች፣ ወዳጆች እንኳን የሰማዕቷ የቅድስት አርሴማ ለእመቤታችን ደብረ ቁስቋም ቅድስት ማርያም ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን የምረቃ በዓል በሰላም አደረሳችሁ።

ውድ የእመቤታችን ወዳጆች ምዕመናን፤ እግዚአብሔር አምላክ ሥራውን የሚሠራበት ጊዜ አለው። በጊዜውም ይህንን ውብ እና ድንቅ የመመስገኛ ቤቱን በእናቱ በቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ሥም እንዲታነፅ ሲፈቅድ ለሥራው ክንውን እኔን እና እናንተን መርጦ ለዚህ ክብር ስላደለን አምላከ ቅዱሳን መድኀኔዓለም ክብር ምስጋና ይድረሰው። አሜን።

በመሆኑም ይህ ቅዱስ ሥፍራ ከተመሰረተበት ከመጋቢት 6 ቀን 2001 ዓ.ም አንስቶ እስከ አሁን በርካታ የልማት ሥራዎች በዚሁ ሥፍራ እንዲሁም በገጠር እና በከተማ ባሉ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ተከናውነዋል። ከእነዚህም ውስጥ በቁጥር 10 አብያተ ክርስቲያናት የታነጹ ሲሆን በአሁኑ ወቅትም ለቤተ ክርስቲያናችን እና ለማኅበረሰቡ ጉልህ አስተዋጽዖ የሚኖራቸው የተለያዩ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ ነው። ይኽም የሆነው አምላከ ቅዱሳን ልዑል እግዚአብሔር መልካም ፈቃዱ በመሆኑ ሲሆን፣ ለዚህ ታላቅ በረከት እኔን እና እናንተን መርጧል እና ቸርነቱን ከእኛ ያላራቀ አምላከ ቅዱሳን ክብር ምስጋና ይድረሰው። አሜን።

የተከበራችሁ ምዕመናን፤ ለብዙዎች ያልሆነ ለኛ ግን በእርሱ ቸርነት በእናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት በሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ ተራዳኢነት ይኽንን ታላቅ እና ታሪካዊ ሕንጻ አስፈፅሞ ለምረቃ ያበቃን፤ እንዲሁም እውነተኛውን እና ትክክለኛውን የሰማዕቷ ቅድስት አርሴማን የገድል መጽሐፍ በሚደንቅ ሁኔታ ተዘጋጅቶ እና ታትሞ በዛሬው ዕለት በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በአባታችን በብፁዕ አቡነ ዮሴፍ እጅ ተባርኮ ለሁላችን እንዲደርስ በመደረጉ እንኳን ደስ አላችሁ። በመጨረሻም ለዚህ ሁሉ መንፈሳዊ ሥራ መሳካት ውድ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች በሙያችሁ፣ በገንዘባችሁ፣ በሀሳባችሁ እና በፀሎታችሁ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳትሉ ሌት ተቀን ያገለገላችሁና የተራዳችሁን ሁሉ ልዑል እግዚአብሔር ይባርካችሁ፤ ወላዲተ አምላክ ቅድስት ድንግል ማርያም በነፍስም በሥጋም አለሁ ትበላችሁ፤ የልቦናችሁን በጎ እና መልካም ሀሳብ ሁሉ ትከውንላችሁ። አሜን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፣ ወለወላዲቱ ድንግል፣ ወለመስቀሉ ክቡር፤ አሜን።
መልአከ ሕይወት ቀሲስ እንደሻው አብርሃ
የይርጋ ዓለም ደ/ታቦር ቅድስት አርሴማ እና ደ/ቁስቋም ቅድስት ማርያም አብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪ

የምረቃ በዓል

አድራሻችን

  • አድራሻ፦ ይርጋ ዓለም ከተማ፣ ሲዳማ ክልል፣ ኢትዮጵያ
  • ስልክ፡ 0913-34 09 75 / 0934-15 03 50
  • ኢሜይል : info@arsema.org
  • የሂሳብ ቁጥር፦ 1000026128548 (የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ) Swift/BIC: CBETETAAXXX
©በኢ/ኦ/ተ/ቤ ሲዳማ ሀገረ ስብከት፣ የደብረ ታቦር ቅድስት አርሴማ እና ደብረ ቁስቋም ቅድስት ማርያም አብያተ ክርስቲያናት